በክልሉ ከ 2.1 ቢሊየን ብር በላይ ሃብት ላስመዘገቡ ባለ ሀብቶች የኢንቨስትመንት ፍቃድ ተሰጥቷል
በሀረሪ ክልል ከ 2.1 ቢሊየን ብር በላይ ሃብት ላስመዘገቡ ባለ ሀብቶች የኢንቨስትመንት ፍቃድ መሰጠቱን የክልሉ ኢንተርፕራይዝና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ምክትል ሀላፊ አቶ ሀምዲ ሰላህዲን ገለፁ።
በሀረሪ ክልል የኢንቨስትመንት ቦርድ እንዲቋቋም በማድረግ በዘርፍ የነበሩ ማነቆዎችን ለመፍታት ትኩረት ተሰጥቶ ሲሰራ መቆየቱን የክልሉ ኢንተርፕራይዝና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ምክትል ሀላፊ አቶ ሀምዲ ሰላህዲን ገለፁ።
ይህም በክልሉ አዳዲስ ኢንቨስትመንቶች እንዲስፋፉ በማድረግ አበረታች ለውጦች እንዲመዘገቡ ማስቻሉን ገልፀዋል።
በተጠናቀቀው የ2017 በጀት ዓመት ከ 2 .1 ቢሊየን ብር በላይ ሀብት ላስመዘገቡ 1 መቶ 11 አዳዲስና የማስፋፊያ ፕሮጀክቶች የኢንቨስትመንት ፍቃድ መሰጠቱንም አክለዋል።
በሌላ በኩል አልሚዎች በኢንቨስትመንት የወሰዱትን መሬት ለታለመለት አላማ እንዲያውሉ ከማድረግ አንፃር የቁጥጥር ስርዓቱ ተጠናክሮ ቀጥሏል ብለዋል።
በዚህም የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወስደው ወደ ስራ ባልገቡ እና ግንባታቸውን ባላጠናቀቁ አልሚዎች ላይ በኢንቨስትመንት አዋጅና ደንብ መሰረት የእርምት እርምጃ መወሰዱን ጠቁመዋል።
ታጥረው የነበሩ 9 ፕሮጀክቶች ወደ ግንባታ እንዲገቡ የተደረገ ሲሆን 27 የመጀመሪያና 3 የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ ሲሰጥ በ 14 አልሚዎች ላይ እግድ ተጥሏል።
ባለፉት ዓመታት በኢንቨስትመንት መሬት ወስደው ያላለሙ 23 አልሚዎች ፍቃድ እንዲሰረዝ መደረጉንም አመላክተዋል።
በሌላ በኩል በክልሉ 1 መቶ 23 ነባር የኢንቨስትመንት ፍቃዶች እድሳት መከናወኑን ገልፀዋል።
በኢንቨስትመንት ህግና ድንጋጌ መሰረት በየዓመቱ ፍቃድ የማደስ ግዴታቸውን ያልተወጡና ሪፖርት ያላደረጉ 2 መቶ 66 ባለሀብቶች ፋይላቸው እንዲጣራ በማድረግ የኢንቨስትመንት ፍቃዳቸው እንዲሰረዝ መደረጉንም አቶ ሀምዲ ሰላህዲን ገልፀዋል፡፡
በክልሉ በኢንበስትመንት ዘርፍ ለመሰማራት ፍላጎት ላላቸው አልሚዎች የክልሉ መንግስት አስፈላጊውን ትብብርና ድጋፍ እንደሚያደርግም አረጋግጠዋል።
0 Comments